
የአዲሽ አዴ ድልድይ
ከላሊበላ ውቅር ዐብያተ ክርስቲያናት አናት ላይ ሕንጻዎቹ ተሰብስበው የሚገኙባቸውን ሁለቱን ቦታዎችን በአንድ በኩል እና እንዲሁም የአዲሽ አዴ ሰፈርን በሌላ በኩል መሀል ለመሀል ለሁለት በመክፈል አዲስ በድንጋይ የተገነባ ድልድይ ተሠርቶ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። ይህን ግንባታ ማከናወን ያስፈለገበት ዋንኛ ምክንያት ታሪካዊ ሕንጻዎቹ ከሚገኙባቸው ጎድጓዳ ቦታዎች አንዱ የላሊበላን ላይኛውና ታችኛውን ክፍል የሚያገናኘውን መተላለፊያ ቦታ ባዶ እንዲሆን ከተደረገ በኋላ ነው። ይህ ቀደም ሲል ተደፎኖ የነበረውን ጎድጓዳ ቦታ የሞላውን አፈርና ድንጋይ ዝቆ ማውጣት ሥራ በታሪካዊው ቦታ ላይ ያሉትን መተላለፊያዎች ወደ ነባር አገልግሎቶቻቸው የመመለስ ዓላማ ያለው የአርኪዮሎጂና የመሬት ገጽታ ወደ ነበረበት የመመለስ ሥራ አንድ አካል ነው። እነዚህ ሥራዎች የተከናወኑት በአርኪዮሎጂ ባለሙያዎች ቡድን እየተመሩ ሲሆን የሥራዎቹ ዝርዝር ወደፊት በሚወጣው ዜና መጽሔት የሚገለጽ ይሆናል።
ይህ ፕሮጄክት በ 2012 ዓ.ም. ሲጀመር ለአፋጣኝ ቅርስን የመጠበቅ እና የላሊበላን ታሪካዊ ቦታ የማጠናከር ሥራ እንዲያገለግሉ የፈረንሳይ የኢትዮጵያ የጥናት ማዕከል (ሲ.ኤን.አር.ኤስ) አንቷን ጋሪክ የተባሉትን የድንጋይ ቅርጽ ማውጣትና የቅርስ ጥበቃ ከፍተኛ ባለሙያን እና እንዲሁም ስለ ቦታው ጥልቅ ዕውቀት ያላቸውን አቶ ኪዳኔ አያሌውን ሥራውን በበላይነት እንዲመሩ መድቧቸው ነበር። በዚህም አቶ ኪዳኔ አያሌው ባስቀመጡት መስፈርት ላይ በመመርኮዝ ለላሊበላ ታሪካዊ ቦታ ዘላቂ ጥገና ለማድረግና ቅርሶቹን ጠብቆ ለማቆየት በተቋቋመው ኮሚቴ አማካይነት 19 የዕደ ጥበብ ባለሙያዎችን (ድንጋይ ቅርጽ ማውጣት ባለሙያዎች፣ ግንበኞች እና አናጢዎች) ተመርጠዋል። አንቷን ጋሪክ ደግሞ እነዚህን ባለሙያዎች የማሠልጠኑን ኃላፊነት ወስደዋል። ሥልጠናው ከበርካታ ሌሎች ነገሮች መካከል በዋንኛነት የድንጋይ ቅርጽ (ስትራክቸር) አወጣጥ የሚያካትት ሥልጠና ሆኖ እነዚህ ሁሉ አንድ ላይ በመተባበር በርካታ ድልድዮችን ሠርተዋል። አቶ ኪዳኔ አያሌው በበኩላቸው ሥራውን እና አስፈላጊውን ሎጀስቲክ አቅርቦት በማስተባበር፣ ቡድኖቹን በበላይነት በመምራት እንዲሁም በላሊበላና በአዲስ አበባ የሚገኙ የመንግሥትና የሃይማኖት ኃላፊዎችን በየቀኑ በማስተባበር ኃላፊነታቸውን ተወጥተዋል።
ለሁለት ዓመት ሥልጠናው ከተሰጠ በኋላ የዕደ ጥበብ ባለሙያዎቹ ራሳቸውን ችለው የአዲሽ አዴ ድልድይን ወደ መገንባቱ ሥራ ገብተዋል።
ሙሉ በሙሉ ከዛው በላሊበላ አካባቢ ከተገኙ አለቶች እየተጠረቡ በወጡ ድንጋዮች የተገነባው አዲሱ የአዲሽ አዴ ድልድይ ከታች ከወለል ጀምሮ ወደ ላይ ስድስት ሜትር የሚወጣ መሠረት ያለው እና ራሱን በራሱ ደግፎ የሚቆም ሙሉ በሙሉ በድንጋይ የተገነባ ዓምድ አለው። የሚያምሩት የድልድዩ አጥሮች አካባቢውን ከድልድዩ ላይ ቆመው በማየት ለማድነቅ ለሚፈልጉ እግረኞች አጥሩን ተደግፈው ማየት የሚችሉበትን ዕድል ይሰጣቸዋል። አዲስ የተቆፈረው ጎድጓዳ ቦታ፣ ድልድዩ እና እንደ አዲስ የተጠገኑት በዙሪያው የሚገኙ ጎጆ ቤቶች ከቦታው የመሬት አቀማመጥ ጋር ሙሉ በሙሉ ያለምንም እንከን እንዲስማሙ ስለተደረጉ በቦታው ላይ ተጨማሪ ውበትን ፈጥረዋል።
የአዲሽ አዴ ድልድይ ሥራ ላይ በከተማዋ የሚኖሩ ሠላሳ የዕደ ጥበብ ባለሙያዎች ተሳታፊ ሆነዋል። እነዚህ ባለሙያዎች ወደፊት የላሊበላ ዘላቂ ጥገና ፕሮጄክት ውስጥ ተሳታፊ የሚሆኑ ናቸው።
ሆኖም ግን በየቀኑ እየተባበሰ በሄደው የጸጥታ ችግር ምክንያት አንቷን ጋሪክ እና አቶ ኪዳኔ አያሌው ለአዲሽ አዴ ድልድይ ግንባታ ወደ ላሊበላ እንደፈለጉት እንዳይጓዙ ስላደረጋቸው የዕደ ጥበብ ባለሙያዎቹ ሥራ ችግር አጋጥሞት ነበር። በነሐሴ ወር 2015 ዓ.ም. በከተማዋ ዙሪያ በሚገኙ ቦታዎች ላይ በኢትዮጵያ መንግሥት ወታደሮች እና በአማራ ፋኖ መካከል ከባድ ውጊያዎች ተደርገውበት ነበር። ላሊበላ ወዲያውኑ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ሥር ከዋለችበት ጊዜ ጀምሮ በከተማዋ ክፍተኛ ውጥረት ነግሥ ነዋሪዎችን ሲያጨንቅ ከቆየ በኋላ በወርሐ ኅዳር ላይ እጅግ ዘግናኝ ውጊያ በከተማዋ ውስጥ እና በዐብያተ ክርስቲያናቱ አካባቢ ተደርጓል።
ከወርሐ ነሐሴ 2015 ዓ.ም. ጀምሮ የዕደ ጥበብ ባለሙያዎቹ ከአዲስ አበባ ከፈረንሳይ የኢትዮጵያ የጥናት ማዕከል ቢሮ በስልክ በሚሰጣቸው መመሪያ እየታገዙ ሥራዎቸውን በመቀጠል የአዲሽ አዴ ድልድይን ግንባታ ሙሉ በሙሉ ለማጠናቀቅ ችለዋል። የቴክኒክ ምክር፣ የተሠሩ ሥራዎችን ጥራት ማረጋገጥ፣ የፋይናንስ እና የሎጀስቲክ ድጋፍ በሙሉ ይሰጥ የነበረው በስልክ ነበር። ባለሙያዎቹ በተወሰነ መልኩ የኢንተርኔት አገልግሎት ማግኘት በሚችሉበት ወቅት ላሊበላ የሚገኘው የዕደ ጥበብ ባለሙያ ቡድኑ ሱፐርቫይዘሮች የሆኑት አምባቸው ተገን እና ሲሳይ መቆያ የሥራ ሪፖርት፣ ፎቶግራፎችን ይልኩ ነበር ወይም ፕላኖችና ቴክኒካል ምክሮችን ይጠይቁ ነበር።
የአዲሽ አዴ ድልድይ የአካባቢው አገር በቀል የቅርስ ጥበቃ ጥበብ፣ የሳይንሳዊ ትብብር እና የላሊበላ ዕደጥበብ ባለሙያዎች ፅናትና አይበገሬነት ታሪክ ነው።

የአዲሽ አዴ ትሬንች
አዲሽ አዴ ፤ በቅ/ላሊበላ በመሀል ከተማው ላይ ከነበሩት ቀዳሚ አና ታዋቂ ሰፈሮች አንዱ ነበር። ከ 2002 እስከ 2011 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ ከዓለም ባንክ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ለቱሪዝም ልማት ሙሉ በሙሉ እስከፈረሰበት ጊዜ ድረስ፤ በሁለቱ አብያተክርስቲያናት ምድብ መካከል በስተምሥራቅ አቅጣጫ በጣም በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ ነበር። መተላለፊያ መንገዶቹ ጠባብና ጥልፍልፍ የበዛባቸው ከመሆናቸው ባሻገር መንቀሳቀስ የሚቻለው በእግር ብቻ ነበር። ከ 1970ዎቹ ጀምሮ አራት ማዕዘን ከጭቃ የተሠሩ ቆርቆሮ ጣራ ያላቸው ቤቶችንና ባህላዊዎቹን የሣር ክዳን ያላቸው ጎጆ ቤቶች አንድ ላይ አጣምሮ ሰፈሩ ጥቅጥቅ ያለ መሆን ጀምሮ ነበር። ከአካባቢው አጎራባች ወረዳዎች የሚመጡ አርሶ አደሮች የሚያዛወትሯቸው በርካታ ትናንሽ ሱቆችንና ቡና ቤቶችም በሰፈሩ ውስጥ ነበሩ። በ1980ዎቹ የመጀመሪያው የቅ/ላሊበላን ቅርሶች የመጠገን እና የማደስ ሥራ በፊንላንድ ፕሮጀክት ሲሠራ በዚህ ሰፈር መውጫ ጫፍ ላይ በፈረሱት ቤቶች ስር የአዲሽ አዴ ትሬንች ትሬንች ተቀብሮ ኑሮዋል። የተቀበረውም ትሬንች ያካባቢው ልጆች የሚጫወቱበት ቦታ ሆኗ ያገለግል ነበር።
ቅ/ላሊበላ የሚገኙት ትሬንቾች ፋይዳ
የቅ/ላሊበላ አብያተክርስቲያን ምክንያቱና ጊዜ አጠቃቀም አሁንም ድረስ አከራካሪ በሆኑ መንግዶች በትሬንችዎች (ትሬንቾች) አንዱ ከሌላው ጋር የተሳሰሩ ናቸው። በ1950ዎቹ ከዓለም ቅርሶች ጥበቃ ፈንድ በተገኘ ድጋፍ የቅ/ላሊበላን ጥገና በበላይነት የመራው ጣልያናዊው ሳንድሮ አንጀለኒ ጊዜ ጀምሮ እነዚህ ትሬንችዎች ትሬንቾች እንደ ፍሳሽ ማስወገጃ መሥመር እንዲያገለግሉ የተዘጋጁ ናቸው የሚል እምነት ነበር። በቅርሶቹ አቅራቢያ ውሃ እንዳይጠራቀም ለማድረግ እነዚህ ትሬንችዎች በዋንኛነት የውሃውን አቅጣጫ እንዲያስቀይሱ የተቆፈሩ ናቸው ተብሎ ይታመን ነበር። በ1950ዎቹ ለቅርሶቹ ጥገና ሥራ ሲሠራ በርካታ ትሬንችዎች ተገኝተዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ ሠራተኞችም በመቶ ሜትር ኩቦች የሚቆጠሩ ደለሎችን ከእነዚህ ትሬንችዎች ሲያጸዱ ቅርሶቹን በአካባቢው ከሚኖር የውሃ እንቅስቃሴ የሚከላከሉ መሆናቸውን ማረጋገጥ ተችሏል። እነዚህ የማጽዳት ሥራዎች በሚሠሩበት ወቅት ተጨማሪ የቅርስነት ይዘት ያላቸው ቁሶች የተገኙ ሲሆኑ የዚህ ማስረጃ ሊሆኑ የሚችሉ በጣም ጥቂት በጥቁርና ነጭ የታተሙ ፎቶግራፎችን ብቻ ማግኘት ተችሏል። በዚያን ጊዜ ምን እንደተገኘ ለማወቅ የሚያስችል ምንም ዓይነት ሪኮርድ ወይም ቅሪተ ቅርስ ማግኘት አልተቻለም።
ሳንድሮ አንጀለኒ ሥራውን ያቆመው በ 1962 ላይ ነው። የተጀመረው ሥራ ሙሉ በሙሉ አልተጠናቀቀም፣ ትሬንቾቹም በሙሉ ተጠናቀው እንዲጸዱ አልተደረጉም። የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን እነዚህን የተጀመሩ ሥራዎች ከቆሙበት እንዲቀጥሉ አደረገ። በዚህ ጊዜም የሁለተኛው ቡድን አብያተቤተክርስቲያናት ሰሜናዊ ትሬንች በሽመልስ ታፈሰና ቡድኑ አማካይነት በቁፋሮ ተገኝቷል። ይሁን እንጂ ዩኔስኮ ሥራውን መልሶ እስኪረከብ ድረስ ይህ ሥራ በድጋሚ ተቋርጦ ነበር። ቅ/ላሊበላን ጠግኖ እና አድሶ ከጉዳት ለመታደግ ይደረግ በነበረው ጥረት ዩኔስኮ የውሃ ማስወገጃ መሠረተ ልማቱ በአግባቡ ሥራውን መሥራቱን ለማረጋገጥ እንዲቻል እነዚህ ከዚህ ቀደም እንዲጸዱ ተደርገው የነበሩትን ትሬንቾች መልሶ የማጽዳት ሥራ አስጀምሮ ነበር።
ይሁን እንጂ የአዲሽ አዴ ትሬንችን ጨምሮ በርካታ ትሬንቾች ጠርዛቸው ብቻ እየታየ በደለል ተሞልተው ተቀብረው እንዲቀሩ ሆኗል።
ከ 13ኛው ክፍለ ዘመን ጀመሮ በላይኛው የቅርሱ ክፍል ውሃ የማቆር ሥራ
የቁፋሮው ሥራ ውጤቱ ከጠበቀነው በላይ ስኬታማ ነበር። በየቅ/ላሊበላ ዘላቂ ጥገና ፕሮጄክት ተደግፎ በአርኪዮሎጂ ትምህርት ዘርፍ የማስተርስ ዲግሪ በያዘው በደሳለ ደጀን እየተደገፈ በሮሜን ማንሶ በ 2015 ዓ.ም. የተከናወነው ሥራ የአዲሽ አዴ ትሬንች ፋይዳ ምን እንደሆነ ደርሶበታል። ከተራ ውሃ ማስወገጃነት ጠቀሜታ ብቻ ሳይወሰን ትሬንቹ ውሃ ለማቆር ተብሎ ዲዛይን የተደረገ ነው። በመሆኑም የውሃ ፍሰት አስተዳደሩ የትሬንቹ ዋንኛ መሠራት ምክንያት ሆኖ እዚህ ላይ ዋና ዓላማው ውሃ በሚጠፋበት ጊዜ እንደ አስተማማኝ የውሃ አቅርቦት ምንጭ ማገልገል ነው። ሌላው በዚህ ቁፋሮ ሥራ ወቅት የተደረሰበት አዲስ ግኝት ትሬንቹ የተሠራበት ዘመን ነው። ይህም ከትሬንቹ ወለል ላይ ከወጣ ደለል የተወሰዱ የከሰል ናሙናዎች ዕድሜያቸው 13ኛው ክፍለ ዘመንን ያመላከቱ ሆነው ተገኝተዋል። ይህም ደለሉ በትሬንቹ ውስጥ ከዚህ ክፍለ ዘመን ጀምሮ መጠራቀም የጀመረ መሆኑን ያመላክታል። ከዚህ ቀደም ትሬንቹ ና አብያተክርስቲያናቱ ከተስሩ (ከተፈለፈሉ) በኋላ የተሠሩ ናቸው ተብሎ ይታመን ነበር። የአዲሽ አዴን ትሬንች በተመለከተ ከቅርሶቹ ጋር እኩል ዘመን ያለው ይመስላል። ከዚህ ዘመን የተሻገረ የተሟላ ጊዜ ቅደም ተክተል (chronostratigraphy) ማግኘት ተችሏል። ከዚህ በተጨማሪ በቁፋሮው ወቅት በርካታ የሸክላ ዕቃ ስባሪዎች ተገኝተዋል። በጥንቃቄ ተሰብስበውና መለያ ተደርጎላቸው በቀይት ተራራ በተደረገው ቁፋሮ ከተገኙት ሴራሚኮች ጋር ጥንታዊ ንጽጽር እንዲደረግባቸው ዝግጁ ሆነዋል።
የቅ/ላሊበላ ዘላቂ የቅርስ ጥገና ፕሮጄክት ክፍል የሆነው የአዲሽ አዴ ትሬንች
የዚህ ትሬንች ቆፍሮ የማጽዳት ሥራ ሁለት ፋይዳ አለው። በመጀመሪያ ደረጃ በደለል መሞላት ምክንያት ለረዥም ጊዜ ተረስቶ የነበረውን የቅርሱን ገጽታ ወደ ነበረበት መመለስ እና ከቅርሱ ላይኛው ክፍል እነዚህ ትሬንችዎች ወለል ብለው እንዲታዩ የማድረግ ዓላማ አለው። በሁለተኛ ደረጃ በሌሎቹ ከዚህ ቀደም ተቆፍረው በነበሩ ትሬንችዎች ላይ የነበረው የአርኪዮሎጂ መረጃ የጠፋ እንደመሆኑ ስትራቲግራፊክ ቆፋሮ በማድረግ ትሬንችው በደለል መሞላቱ ተፈጥሯዋዊ ስለመሆኑ እና ምን ዓይነት ቅርሶች እንደሚገኙ በተመለከተ የሚገኘውን መረጃ በጥንቃቄ የመመዝገብ ሐሳብ ያለው ነው። ይህ ከሆነ የአዲሽ አዴ ትሬንች ለምን ዓላማ እንደተሠራ ለመረዳት የሚያግዝ ይሆናል።
ከመድኃኔ ዓለም ቤተክርስቲያን እስከ አማኑኤል ገዳም ድረስ ከጫፍ እስከ ጫፍ ሲለካ የአዲሽ አዴ ትሬንች 125 ሜትር ርዝማኔ አለው። ካለው አማካይ የ 7 ሜትር ጥልቀት ወደ 6.50 ሜትር ስፋት የሚሆነው ደለሉ ተቆፍሮ ወጥቶለታል። የቁፋሮ ሥራው 60 ቀናትን የፈጀ ሲሆን በየ 15 ቀናቱ በፈረቃ ይሠሩ የነበሩ 800 ሠራተኞችን አሳትፏል። በ 4 ከቅ/ላሊበላ ቤተክርስቲያን እና ከቅ/ላሊበላ የባህልና ቱሪዝም ቢሮ የተውጣጡ ሠራተኞች በበላይነት የሚመሯቸው እኩል ቁጥር ያላቸው 200 ወንድና ሴት ሠራተኞች በሳይቱ ላይ በየቀኑ እየሠሩ ነበር። እነዚህን ሠራተኞች በመቅጠር ሂደቱ ላይ የቅ/ላሊበላ ዘላቂ ጥገና ፕሮጄክት ቡድን ከቅ/ላሊበላ አራቱ ቀበሌዎች የተውጣጡ የአካባቢው ባለሥልጣናት ጋር በትብብር ሠርቷል። በ 2012 ላይ የቱሪዝም እንቅስቃሴ በአካባቢው ሙሉ በሙሉ በመቆሙ ምክንያት እና ከ 2015 ክረምት ጀምሮ በከተማዋና በአጎራባች አካባቢዎች የሚኖሩ አርሶ አደሮች በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በአጠቃላይ በአማራ ክልል ውስጥ በነበረው ግጭት ክፉኛ ስለተጎዱ ፕሮጄክቱ ምንም እንኳ ለአጭር ጊዜ የሚቆይ ቢሆንም በቅ/ላሊበላ ውስጥ ክፍያ የሚያስገኝ ሥራ ሊሠራ የሚችልበትን ዕድል ፈጥሮላቸዋል። ከቤተክርስትያናቱ አጠገብ ይደረግ የነበረው የትሬንች ቁፋሮው ለታሪካዊው ቅርስ የሚደረግ ቀና የእንክብካቤ ሥራ መሆኑን ሠራተኞቹ ተረድተውታል። በዚህም ምክንያት በቅ/ላሊበላ ታሪክ መጥፎ በሚባለውን ጊዜ ሥራው በተሳለጠ መንገድ እንዲከናወን የበኩሉን አስተዋጽኦ አድርጓል። በመሆኑም ከትሬንችው ተቆፍረው የወጡት ደለልና ድንጋዮች በአሮጌው የአዲሽ አዴ ሰፈር ውስጥ ለመሬት ማስተካከልና ማጠናከር ሥራ ጥቅም ላይ እንዲውሉ ተደርገዋል።

ቀይት ተራራ እና በቅ.ላሊበላ እየተከናወነ ያለው አርኪዮሎጂያዊ ምርምር
ከዐብያተክርስቲያናቱ ጥራቢዎችን በጥንቃቄ ማስወገድ ሥራ
የቅዱስ ላሊበላ አብይተክርስቲያናት፤ የውሃ መፈሳሽወቹ እና የውስጥ ለውስጥ መተላለፊያወቹ በሚጠረቡበት ጊዜ፣ እየተጠረበ የወጣው በኋላም በቅርሶቹ አካባቢ የተከመረው እጅግ በጣም ብዙ ጥራቢ፣ ኮረብታ መሰል ቁልሎችን በጊዜ ሂደት ፈጥሮ እንደነበረ በላሊበላ እየተከናወነ ያለው አርኪዮሎጂያዊ ምርምር ስራ ያሳያል። ከነዚህ ኮረብቶች መካከል አንዳንዶቹ ዛሬም ድረስ በቦታው ላይ ይገኛሉ። ከበርካታ ጥናት በኋላ ከነዚህ ኮረብቶች መካከል አንዱ ኦርኪዮሎጂያዊ ምርምር እንዲደረግበት ተመርጠ። ይህ የተመረጠው ቦታ በሁለተኛው የዐብያተስቲያናቱ ቡድን ውስጥ የገኛል።
በዚህ የጥናት ቦታ አካባቢ የተደረጉት መነሻ ኦርጂዮሎጂያዊ ጥናቶች ካርቦን-14 (ሲ14) በመጠቀም በተገኘ ታሪካዊ የቤት መሰረት ከ10ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ እስከ 11ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ባለው ጊዜ ውስጥ እንደተሠራ አረጋግጠዋል። (ካርቦን-14 የቀን ግመታ በአንድ የተወሰነ ወጥ ልኬት የሚበሰብሱ (ኦርጋኒክ የሆኑ) ነገሮች ላይ ያለውን ኮርቦን-14 የተባለ ራዲዮአክቲቭ ኢሶቶፕ (radioactive isotope) መጠን በመለካት ዕድሜያቸው ስንት እንደሆነ ለማወቅ የሚያገለግል ሳይንሳዊ ዘዴ ነው።) በከፊል የወደቀው የዚህ ግንብ የተወሰነ ክፍል ወደ ገብሪኤል-ሩፋኤል ቤተክርስቲያን በሚወስደው መንገድ ላይ አሁንም በዓይን ለማየት ይቻላል። የቁፋሮ ሥራውን በመቀጠል ያተኮረ ከመርቆርዮስ ቤተክርስቲያን ፊት ለፊት ባለው ኮረብታ ላይ ነበር። በዚህ ታሪካዊ ቦታ ላይ በርካታዎቹን ዐብያተክርስቲያናት ከሚያገናኘው መንገድ በመነሣት ሥራው በቀጥታ የጥራቢ ክምሩን መቆፈር ነበር። ከዐለት የተጠረበ ክብ ቅርጽ ያለው ነገር ቀስ በቀስ ለአርኪዮሎጂስቶቹ ይታያቸው ጀመር። ሲ14 የቀን ግመታ እነዚህ ግንባታዎች ከ11ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ እስከ 12ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ የተሠሩ መሆናቸውን አመላክቷል፤ ይህም ንጉሥ ላሊበላ ከመንገሣቸው በፊት ጥቂት ዐሥርት ዐመታትን ቀደም ብሎ የሆነ ነው። ቁፋሮ እየተከናወነበት ያለውን ቦታ ክፍት እንደሆነ ለመተው ከሚመለከታቸው ባለሥልጣናት እና የላሊበላ ሕዝብ ፈቃድ ከተገኘ በኋላ ቁፋሮው እየሰፋ ሄደ። በዚህ ጊዜ ቁፋሮው የተከናወነው ከኮረብታው አናት ጀምሮ የተለያዩ ስትራቲግራፊክ ልባሶችን እያገኙ ወደ ታች በመውረድ ነበር።
አርኪዮሎጂያዊ ቁፋሮው የተመራው በሮማ ሜንሳ (Romain Mensan) ነበር። ዶ/ር አለባቸው በላይ እና ዶ/ር ህሉፍ በርሔን ጨምሮ በርካታ ኢትዮጵያዊያን ተመራማሪዎች እንዲሁም ከሌሎች በርካቶች መካከል በጥቂት እነ ዶ/ር ማሪ ሎር ዴራ /Dr. Marie-Laure Derat/፣ ዶ/ር አን-ሊዝ ጉዦ /Dr. Anne-Lise Goujon/፣ ዶ/ር ፍራንሷ ዣቪየር ፎቬል /Dr. François-Xavier Fauvelle/፣ ማኖ ሩታዮ /Manon Routhiau/፣ ዶ/ር ካሮሊን ሮቢን-ብሩኔ /Dr. Caroline Robion-Brunner/ የተባሉ ፈረንሳዊያን ተመራማሪዎች በምርምሩ ላይ ተሳታፊዎች ነበሩ። ከዚህ በተጨማሪ የወልዲያ ዩኒቨርስቲ (ላሊበላ ካምፓስ) የማስተርስ ዲግሪ ተማሪዎች በአርኪዮሎጂያዊ ቁፋሮ ከሚማሩት ትምህርት እንደ አንድ አካል ሆነው በጥናቱ ላይ ተሳታፉ እንዲሆኑ ተደርገዋል። በቁፋሮው የመጀመሪያው ውጤት በርካታ ክብ ቅርጽ ያላቸው ስትራክቸሮች ተገኝተዋል። እነዚህ ስትራክቸሮች ከ14ኛው ክፍለ ዘመን እስከ 16ኛው ክፍለ ዘመን የነበረውን ቦታው ሙሉ በሙሉ እርግፍ ተደርጎ የተተወበትን ዘመን ሳይጨምር ከ11ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ እስከ 18ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ እንደተገነቡ ለማረጋገጥ ተችሏል። ከ18ኛው ክፍል ዘመን በኋላ አጠቃላይ ቦታው በፍርስራሾች ተውጦ ነበር። የነዚህ ስትራክቸሮች ጠቀሜታ ምን እንደነበረ አሁንም ድረስ አልታወቀም። ይሁን እንጂ በእያንዳንዱ የቆፋሮው ደረጃ ላይ ማንደጃዎች፣ የቤት ቁሳቁስ ስብርባሪዎች (በዋንኛነት ሴራሚክ መጠጫና መመገቢያዎች)፣ ጥቂት ዶቃዎች እና የእንስሳት ዐፅሞች ተገኝተዋል። በመሆኑም ይዞታዊ መንፈሳዊ ቦታ እንዳልሆነ መገመት ቢቻልም የእነዚህ ስትራክቸሮች ወደ ዐብያተ ቤተክርስቲያኒ መጠጋት (ቢያንስ ከ13ኛው ክፍለ ዘመን ወዲህ) ከቤተክርስቲያናቱ እና ይገለገልባቸው ከነበረው ማኅበረሰብ ጋር አንዳች ግንኙነት ወይም ሚና እንደነበራቸው ይጠቁማል።
ማኅበረሰብ አቀፍ አርኪዮሎጂ ጥናት፦ ከአርኪዮሎጂያዊ ጥናት በተጨማሪ ታሪካዊ ትርክቶችን ዳግመኛ መፍጠር
በቅዱስ ላሊበላ እየተከናወኑ ያሉት አርኪዮሎጂያዊ ቁፋሮች ከአካባቢው ማኅበረሰብ እና ቅርሶቹን በመጠበቅ ረገድ ኃላፊነት ካለው ባለሥልጣን መሥሪያ ቤት ይሁንታ ፈቃድ ካገኘ በኋላ የተጀመረ ፕሮጄክት ነው። ይሁን እንጂ ይህ የተሰጠው ይሁንታ የዕድሜ ልክ አይደለም። ቀጣይነቱ በታሪካዊው ቦታ ላይ በሚያስገኘው ፋይዳ እና ወደፊት በሚኖረው ሚና ላይ የተንጠለጠለ ነው። የሚደረጉት ውይይቶች በርካታ እና አስጨናቂ ናቸው። በዚህም በኪዳኔ አያሌው የተቀየሰውን «ማኅበረሰብ አቀፍ አርኪዮሎጂ ጥናት» በሥራው ላይ በቅንጅት ተጣጥሞ እንዲሠራ ከሚል ውሳኔ ላይ በመጨረሻ ተደርሷል። ይህ ዘዴ ከላሊበላ ነዋሪዎች ጋር ተባብሮ ለመሥራት የሚደረገውን ጥረት ወጥነት ያለው ቅርጽ እንዲይዝ አድርጓል። ከሁሉም በፊት በአርኪዮሎጂያዊ ጥናት ቦታው ላይ በቁፋሮው ሂደት ተቀጥረው የሚሠሩት ሠራተኞች ቁጥራቸው ወደ 70 ይይሚደርሱ ከአካባቢው የተውጣጡ ግለሰቦችን እንዲያካትት ዘዴው መንገድ ጠርጓል። በዚህም የቤተክርስቲያን አባቶች፣ የቤተክርስቲያን ጠባቂዎች፣ በተለያየ የዕድሜ ክልልና ማኅበራዊ አቋም ላይ የሚገኙ የቀን ሠራተኞች፣ እና የወልዲያ ዩኒቨርስቲ (ላሊበላ ካምፓስ) የማስተርስ ዲግሪ ተማሪዎች በአርኪዮሎጂያዊ ቁፋሮ ከሚማሩት ትምህርት እንደ አንድ አካል ሆኖ በፕሮጄክቱ ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑ አድርጓል። የላሊበላን ብዝኃነት የሚወክሉ አነስተኛ ናሙና ናቸው ብሎ መናገር ይቻላል። በዚህ ወቅት ሁለት ዓላማዎችን ከግብ ለማድረስ ተወጥኖ ነበር። በመጀመሪያ ደረጃ በመስኩ ጥናት እያደረጉ ያሉትን ተማሪዎች በቁፋሮው ሥራ ላይ በተወሰነ ደረጃ ራሳቸውን ችለው በኃላፊነት በሥራቸው ሠራተኞችን ይዘው መሥራት እንዲችሉ የማብቃት ዓላማ ነው። ተማሪዎች ተሳታፊ እንዲሆኑ መደረጉ አርኪዮሎጂስቶቹ ምን ለማወቅ እየሠሩ እንዳሉ በቀላሉ ለማኅበረሰቡ ግንዛቤ ለማስጨበጥ እና ቡድኑም ትክክል ነው ብሎ ባመነበት አቅጣጫ ምርምሩን በነጻነት ለማድረግ የሚችልበትን ዕድል ፈጥሮለታል። ሁለተኛው ዓላማ ደግሞ ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር በመመካከር ለአርኪዮሎጂያዊ የጥናት ቦታው ስያሜ መስጠት ሲሆን ይህም በላሊበላ ዙሪያ ካለው ታሪካዊ ትርክት ጋር የሚጣጣም ስም እንዲገኝ ለማድረግ አስችሏል።
ይህ ስያሜን በተመለከተ በተደረገው ውይይት ሠራተኞችን እና መላውን የላሊበላ ማኅበረሰብ በቀጥታ ተሳታፊ ለማድረግ የሚያስችል ኃያል መሣሪያ መሆኑን በተጨባጭ አረጋግጧል። የቁፋሮው ግብ በቤተክርስትያናቱ ዕድሜ ጠገብነት የተነሣ እየጠፋ የነበረውን የመጀመሪያውን የመሬት አቀማመጥ እንደነበረ ለመመለስ ነው። ሁሉም ሰው ይህ ቦታ ቀደም ሲል ስም እንደነበረው ቢያምንም ስሙ ምን ይባል እንደነበረ ሊያስታውስ የሚችል ሰው ግን ሊገኝ አልተቻለም። በተከታታይ በተደረጉ ውይይቶች እና ምክክሮች አማካኝነት በስተመጨረሻ ቦታውን የሚመጥን ስም የተገኘ ሲሆን ይህም ስም በነዋሪዎች እና በአካባቢው ሃይማኖታዊ እና ቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣናት ይሁንታን አግኝቷል። በመሆኑም አርኪዮሎጂያዊ የጥናት ቦታው አሁን “ቀይት ተራራ” በመባል ይታወቃል። ቀይት የምትባለው ሴት ላሊበላ በዚህ ቦታ ላይ ቅዱስ ላሊበላ ዐብያተክርስቲያኑን እንዲያነጽ በታየው ራዕይ መሠረት ወደ ቦታው ሲመጣ መሬቱን የሸጠችለት ባለርስት እንደነበረች በገድለ ላሊበላ ላይ ተጽፎ ይገኛል። በመሆኑም ቦታው በስሟ «ቀይት ተራራ» ተብሏል።
ማኅበረሰብ አቀፍ አርኪዮሎጂ ጥናቱ የቦታ ስም ከማስገኘትም በዘለለ ኦርኪዮሎጂያዊ ቁፋሮው ከንጉሠ ነገሥቱ ዘመን በፊት የነበሩ ይዞታዎች እንደነበሩ ፍንጭ እንደመስጠቱ የዚህችን ሴት ታሪክና ላሊበላ ከመምጣቱ በፊት በዚህ ቦታ የነበረውን ታሪክ እንደገና እንዲወሳ ዕድሉን ፈጥሯል።